የአዲስ ኪዳን ክብር ከብሉይ ኪዳን ክብር ይልቃል

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በዚሁ ጉዳይ ላይ በ፪ኛው ወደ ቆሮንጦቶስ ሰዎች መልዕክቱ ላይ ፣ በምዕራፍ ፫ ከቁጥር ፯ እስክ ፲፩ በጻፈው አጭር መግለጫ ላይ “..የፊተኛው ኪዳን አገልግሎት የሞት አገልግሎት ነው” ብሎ የመልዕክቱን መነሻ ቃል አስቀምጦ እናገኘዋለን ።  

ሐዋርያም አስከትሎ ደግሞ የአዲስ ኪዳን አገልግሎት ግን የመንፈስ አገልግሎት ነው እያለ የአዲሱን ኪዳን ክብር ከፍ አድርጎ እንደጻፈም እናነባለን። 

እንደገና ወረድ ብሎ በቁጥር ፱ ላይ ስለ ብሉይ ወይም ስለ ፊተኛው ኪዳን አገልግሎት ሲናገር “የኩነኔ አገልግሎት ነው” ብሎ ሲያበቃ ፤ የአዲሱ ኪዳን አገልግሎት ግን “የጽድቅ አገልግሎት ነው” ብሎ ትምህርቱን እስከ ወዳኛው እየከፋፈለና አጠንክሮ ጽፎ እናነባለን ።

የምዕራፉ ክፍል እንዲህ ይላል ፤ ቆሮ ፪ ፥ ፯ – ፲፩ ፥ “… ያ በፊደላት በድንጋዮች ላይ የተቀረጸ የሞት አገልግሎት በክብር ከሆነ የመንፈስ አገልግሎት እንዴት ይልቅ በክብር አይሆንም ? …”  ይላል ።

ስለዚህ በእውነት የአዲሱ ኪዳን ከፊተኛው ወይም ከብሉይ ኪዳን እንደሚልቅ ሐዋርያው እንዳረጋገጠልን እንረዳለን ።

መቼስ አንድ አገልግሎት ወደ ሞት የሚወስድ አገልግሎት ሆኖ ከተገኘ በማናቸውም አመለካከት አገልግሎቱን በፍጽም እንደማይፈልግ እሙን ነው ። 

ስለዚህ እንደ ሐዋርያው መልዕክትና አገላለጽ የብሉይ ኪዳን አገልግሎት እውነት “የሞት አገልሎት ሆኖ የተገኘው በእንዴት ዓይነት መንገድ ነው ?”    ወደሚል ጥያቄ ያመራናል ።  የሞት አገልግሎት ማለት እኮ ወደ ሞት የሚያደርስ አገልግሎት ማለት ነው ። በሌላ አነጋገር አገልግሎቱ  የሞት አገልጋይ ነው ፤ ሕይወት ያለውን ሁሉ መርቶ መርቶ ለሞት የሚስረክብ ጥሩ የሞት አሽከር ነው — ማለት ነው እኮ ።

Flower with Green Background

 

ግን ይህ እንዴት እንደሆነ ምክንያቱ ሲብራራ እንደሚከተለው ይገለጻል ።


እንደሚታወቀው የብሉይ ኪዳን መሠረት በኪዳኑ ውስጥ የተደነገጉትን ትዕዛዛቱን ማዕከላዊ ያደርጋል። በተጨማሪ እያንዳንዱ ትዕዛዝ እያንዳንዱ ምንም ሳይጎል እንዲፈጸም ይጠበቃል ።

ይህም ማለት ከትዕዛዛቱ አንዲት ጭረት እንኳ ሳትቀር እንዲትፈጸም የትዕዛዙ አጠቃላይ ትዕዛዝ ነው።

ይህ የሆነበት ምክንያት ግልጽ ነው — ትዕዛዙቱን የሰጠው ራሱ እግዚአብሔር ጻድቅ ነውና ፣ የእግዚአብሔር ሙሉ ሞገስ ለማግኘት አንዲቷን ትዕዛዛት አጉድሎ ትዕዛዙን ሁሉ መቶ ከመቶ በሙላት እንደፈጸመ ሆኖን በእርሱ ፊት መገኘት አይሆንምና ። እግዚአብሔር ጻድቅ ስለሆነ ኪዳኑን ሙሉ መፈጸም ግዴታ ነው ። ትዕዛዙን ሳይንፈጸም በጻድቁ በእግዚአብሔር ፊት ማንም ሰው ቢሆን የእግዚአብሔር ሙሉ ሞገስና የልቡን ደስታ ያስገኛል ማለት አይሆንም ።

እዚህ ላይ ምናልባት ሰው በተለምዶ አስተሳሰብ “እግዚአብሔር መሐሪም ነውና ፤ ሰው ትዕዛዛቱን ሁሉ ሳይፈጽም ቢቀር እንኳ ፤ እግዚአብሔር ሁሉን ያውቃልና በፈጠራቸውም በፍጥረቱ ላይ አይጨክንምና እኔ የተቻለንን ብናደር ይበቃል ” ብዬ አስብ ይሆን ?

አዎን ፤ እርግጥ እግዚአብሔር መሐሪ ነው ፣ ምሕረትን ያደርጋል ።

ግን ደግሞ አንተ ሰው ፣ ትዕዛዛቱን ገና ከመጀመሪያው ሲሰጥ እኮ ትዕዛዙ እንዲፈጸምለትም አውቆና አስቦ ነው እንጂ አለበለዚያማ ትዕዛዙን መስጠቱ ምን ትርጉም ይኖረዋል ብለህ ታስባለህ ? እንዳዛስ ከሆነ ትዕዛዙ መስጠቱ የከንቱ ነገር አይሆንምንም ? እረ ፤ እግዚአብሔር ከንቱ ነገር አያደርግም ፤ ኪዳኑን የሰጠው በእርግጥ እንዲፈጸም እንጂ ፤ ለሌላ አይደልም ። እግዚአብሔር መቼም ቢሆን ከባሕርዩ ለዘላለም ጽድቅ ነውና እንዲህ ያለ ነገር አያደርግም ።

ይልቁኑ ትዕዛዛቱ ሙሉ በሙሉ ከአልተፈጸሙ አደጋ እንዳለው ማወቅ ይበጃል ። ይህንን አደጋ ችላ ማለትም ሆነ አለማወቅ ትርፉ ከእግዚአብሔር ጋር መጣላት እንደሚሆን አይጠረጠርም ። አደጋውም ከእግዚአብሔር መንገድ መራቅና ፍርድን እንደሚያስከትል በቅዱስ ቃሉ ደጋጋግሞ ተጽፏል ።

በመጽሐፍ ቅድስ —ትዕዛዙን የማይፈጽምን ሰው እግዚአብሔር እንደማያከብረው ተናግሯል ። ይህንን ከልብ እንዲታውቅ አስፈላጊ ነው ። ትዕዛዙን የማይከብሩ ሁሉ የእግዚአብሔር ክብር ጎድሎቸዋል ብሎ በቃሉ መስክሯል ። ሮሜ 3፡13 ይመልከቱ ።

ስለዚህም የብሉይ ኪዳን መሠረት የሆኑትን ትዕዛዛቱን ሰው ሁሉ ምንም ሳያጓድል እንዲፈጽም ግዴታ እንደሆነ እናያለን ።

ወደ ትዕዛዙ በዝርዝር ስንመለከት ፤ ትዕዛዛቱ በራሳቸው በጎና መልካም እንደሆኑ እናያለን ። ለምሳሌ አትስረቅ የሚለውን ትዕዛዝ ብናይ በቂ ነው ፤ ታዲያ ሰው ሁሉ ይህች ትዕዛዝ እንኳ መልካም እንደሆነ ያውቃል ። ሌሎቹንም እንዲሁ መርምሮ ማየት ይቻላል ። እያንዳንዱ ትዕዛዛት ትክክልና መልካም ነው ።

ይህ እውን ሆኖ ሳለ ግን ማንም ሰው ትዕዛዙን ሙሉ በሙሉ መፈጸም እንደማይችል ይታወቃል ። እንኳን መቶ በመቶ ቀርቶ ገሚሱን ትዕዛዝ እንኳን መፈጸም ይቻላልን?

ለማንኛውም ትዕዛዛቱን ሙሉ በሙሉ በመፈጸምና አስፈላጊነትና የአፈጻጸም አቅም ማነስ መካከል ያለውን ክፍተት አጎልቶ ከኪዳኑ የተነሳ እናያለን ።

በሌላ አነጋገር ብሉይ ኪዳን “ሰው ሆይ ፣ አንተ እግዚአብሔርን ደስ የማሰኘት አቅም የለህም” ብሉ የሚያመለክት መብራትና አመልካች እንደሆነ ይታወቀን ። ብዙዎች እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ትንሽም ቢሆን አቅም እንዳላቸውን ያስባሉ ። የፊተኛው ኪዳን ግን ማናችንም ብንሆን በራሳችን እርሱን ደስ ማሰኘት እንደማንችል ከምር እንዲገባን ያስረዳናል ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የሞት አገልግሎት ነው ያለበትን ምክንያት ነገሩን እንዲዚህ አገናኝቶን ነው ። ምንም እንኳ አገላለጡ ትንሽ ግራ የሚያጋባ ቢመስልም ፤ እውነቱ እንደሆነ ግን እንገነዘባለን ።


የአዲሱ ኪዳን ግን በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ወደ ሕይወት የሚወስድ አገልግሎት ስለሆነ እውነትም ይልቃል ።